“የሽብር ወንጀል ወይም ሽብርተኛነት ፖለቲካ ሳይሆን የህልውና ጉዳይ ነው። አሸባሪነት ላይ ዓለም በሕብረት ነው የሚሰራው። ስለዚህ ጉዳዩ ይመለከተናል ” በማለት ዜናውን የሰሙ የሻዕቢያን የኋላ ታሪክ በማስላት ኢትዮጵያም ልታጤነው እንደሚገባ እየገለጹ ነው። ይህ የተነሳው አሜሪካ ሽብርን ለመከላከል በቋሚነት ቪዛ ከተከለከሉ አገራት መካከል አንዷ መሆኗን ተከትሎ ነው።
አሜሪካ ጉዳት ሊያደርሱባት የሚችሉ የውጭ አገር ዜጎችን ለመከላከል በሚል መርጣ ወደ ምድሯ እንዳይገቡ ከከለከለቻቸው አስራ ሁለት አገራት ስም ዝርዝር ውስጥ ኤርትራ ተካታለች። አሜሪካ የኤርትራን የጎዞ ሰነድና መታወቂያ የሚሰጠውን ባለስልጣን ወይም ተቋም ብቃት ጥያቄ ውስጥ እንደምታስገባና፣ የኤርትራ መንግስት የሰዎችን የወንጀል ሪኮርድ ዝግ ማድረጉን የዕግዱ ምክንያት ከሆኑት መካከል ጠቅሳለች።
“ጉዳት ሊያደርሱብን የሚፈልጉ ሁሉ ወደ አገራችን እንዲገቡ አንፈቅድም” ያሉት ዶናልድ ትራምፕ የፈረሙት አዲስ አዋጅ አስራ ሁለት አገራትን ለይቶ ያስቀመጠ ነው። የዕግዱ ዝርዝሩ ወደፊት መሻሻል ተደርጎበት ሌሎችንም ሊያካትት እንደሚችል ተጠቁሟል።
የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የአስራ ሁለት ሀገራት ዜጎች ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ የሚከለክለውን እግድ የፈረሙት ረቡዕ ዕለት ነው። ይህ የኢሳያስ አፉወርቂ ኤርትራን ዜጎች ያካተተው የዕግድ እርምጃ ያስፈለገው “የውጭ አገር አሸባሪዎችን” የተባሉትን እና ሌሎች የጸጥታ ስጋቶችን ለመከላከል እንደሆነ ተገልጿል።
መመሪያው ትራምፕ በሁለተኛው የስልጣን ዘመናቸው መጀመሪያ የጀመሩት የኢሚግሬሽን እርምጃ አካል ሲሆን ይህም “የወሮበሎች ቡድን አባል ናቸው” ተብለው የተጠረጠሩ በመቶዎች የሚቆጠሩ ቬንዙዌላውያን ወደ ኤል ሳልቫዶር እንዲሰደዱ መደረጉን እና የአንዳንድ የውጭ አገር ተማሪዎችን ምዝገባ ለመከልከል፣ እንዲሁም ለማስወጣት የተጀመረውን እንቅስቃሴ እንደሚያካትት የሮይተርስ ዘገባ ያስረዳል።
ዶናልድ ትራምፕ ” አዋጁ ብሔራዊ ደህንነታችንን ያጠናክራል ” ያሉ ሲሆን ሃገራቱ ስለ ዜጎቻቸው አስፈላጊውን መረጃ ማቅረብ የማይችሉ መሆናቸው ደግሞ ለዕግዱ አንዱና ዋናው ምክንያት ሆኖ ቀርቧል።
ሰባት የአፍሪካ አገራት የተካተቱበት ዕግድ የተጣለባቸው አገራት ኤርትራ ፣ አፍጋኒስታን ፣ ማይናማር ፣ቻድ፣ ሪፐብሊክ ኦፍ ኮንጎ፣ ኢኳቶሪያል ጊኒ፣ ሃይቲ ፣ ኢራን፣ ሊቢያ፣ ሶማሊያ፣ ሱዳን፣ የመን ናቸው።
በእገዳው የአሜሪካ ኃይልን የሚደግፉ የአፍጋኒስታን ዜጎች እና ልዩ ቪዛ ያላቸው፣ ዲፕሎማቶች፣ አትሌቶች እና የጥምር ዜግነት ያላቸውን እንደማያካትት ተጠቁሟል።
የኢምግሬሽን ታሪካቸው ተገምግሞ ዕግድ የተጣለባቸው እነዚህ አገራት ብዙ ጊዜ ከአሜሪካ ዜጎቻቸው እንዲወጡ ሲደረግ ለመቀበል ፈቃደኛ ያልሆኑ፣ ከዚህም በላይ በተጨማሪ የቪዛ ቆይታቸው ከሚፈቅድላቸው ጊዜ በላይ የሚቆዩ መሆናቸው በዕግዱ እንደ ሰበብ የተመለከቱ ነጥቦች ናቸው።
እገዳው ሰሞኑን በቱሪስት ቪዛ ገብቶ ከጊዜው በላይ የቆየ የግብፅ ዜጋ በኮሎራዶ ያደረሰውን ጥቃት ተከትሎ የተወሰነ እንደሆነ ተመልክቷል።
የኋይት ሃውስ ቃለ አቀባይን በመጥቀስ የተለያዩ የዜና ምንጮች እንዳሉት ፕሬዚዳንት ትራምፕ ሌሎች ወንጀለኞች አሜሪካ ገብተው ጥቃት እንዳይጎዱን የመከላከል ስራ እየሰሩ መሆኑን አመልክተዋል።
ከአስራ ሁለቱ አገራት በተጨማሪ የብሩንዲ፣ የኩባ፣ የላኦስ፣ የሴራሊዮን፣ የቶጎ፣ የቱርክሜኒስታን እና የቬንዙዌላ ዜጎች ከፊል የዕገዳ መመሪያ እንደወጣባቸው ከዋይት ሃውስ ከወታው ዘገባ ለመረዳት ተችሏል።
ዕግዱን አስመልክቶ ከዋይት ሐውስ የተሰራቸው መግለጫ የኤርትራ ዜጎች ላይ ወደ አሜሪካ ምድር እንዳይገቡ የተጣለውን ዕገዳው አስመልክቶ ምክንያቱን በዝርዝር አስቀምጧል።
ዋይት ሃውስ እንዳለው የጉዞ ሰነድና መታወቂያ በሚያዘጋጁት የኤርትራ ማዕከላዊ ባለስልጣን ወይም ተቋማት ብቃት ላይ የአሜሪካ መንግስት እምነት የለውም። ወይም ጥያቄ አለው።
መረጃው የኤትራን ዝግነት ለዕግዱ በምክንያትነት ያነሳል። የኤርትራ መንግስት የዜጎቹን የወንጀል ታሪክ ለአሜሪካ ድብቅ ማደረጉን አግባብ ሆኖ አልተገኘም። መረጃውን የሚተነትኑ እንደሚሉት ሻዕቢያ በባህሪው ዝግ በመሆኑና መተዳደሪያው ሁሉ ከወንጀል ጋር የተያያዘ በመሆኑ አሜሪካ ይህንን ጉዳይ ማመላከት ፈልጋ ነው። ይህ ገለጻ በቀርቡ በአልጃዚራ ላይ የተቃውሞ ጽሁፍ ሲያሰራጩ ሻዕቢያን ከወሮበላ ጋር ካመሳሰሉት የቀድሞ ፕሬዚዳንት ዶክተር ሙላቱ ማብራሪያ ጋር ተያያዥ እንደሆነ ያመለክቱም አሉ።
ሌላው ዋይት ሃውስ እንደ ምክንያት ያነሳው ኤርትራ ከአሜሪካ የሚባረሩ ዜጎቿን ለመቀበል ፈቃደኛ አለምሆኗን ነው። ከዚህ የእምቢተኛነት ሪኮርድ በተጨማሪ፣ በተለያዩ ቪዛዎች ወደ አሜሪካ የገቡ ኤርትራውያን ከተፈቀደላቸው ጊዜ በላይ አሜሪካ መቆየታቸው ተወስቷል። በመቶኛ ተሰልቶ ተቀምጧል። በውጤቱም የኤርትራ ዜጎች በስደተኝነትም ሆነ ከዚያ ውጪ ወደ ዩናይትድ ስቴትስ እንዳይገቡ ሙሉ ለሙሉ ታግደዋል።
ክከነጮቹ አቆጣጠር ጁን 9 ጀምሮ ተግባራዊ ይሆናል የተባለውን ይህን ዕግድ የአፍሪካ ህብረትና አንዳንድ አገራት፣ እንዲሁም የመብት ተከራካሪ መሆናቸውን የሚናገሩ እየተቹት ነው።
ገለልተኛ አሳቢዎች ደግሞ ሕዝብና መንግስታት መለያየት እንዳለባቸው በመጥቀስ በጅምላ ኤርትራዊያንን ጨምሮ የሌሎች አገር ዜጎችን አሜሪካ ማገዷን አልወደዱትም። ትክክል እንዳልሆነም እየተናገሩ ነው። አያዘውም ከኢምግሬሽን ሰነድ አሰጣጣ ጋር በተያያዘ አሜሪካ እጅግ የመረረ አቋም በመያዟ መንግስት በሌብነት የሚታማውን ተቋም ሊመረምር እንደሚገባ ጠቁመዋል።
አሸባሪነትን አስመልክቶ አውሮፓም ሆነ ሌሎች አገራት ተመሳሳይ አቋም ሊወስዱ ስለሚችል ኢትዮጵያ የጉዞ ሰነድ በሌብነት በሚቸበችቡ ባለስልታናትና ኔት ወርካቸው ላይ ጥብቅ ቁጥጥር እንድታደርግ ያሳሰቡ አካላት የሰጡትን አስተያየት አከታትለን እናትማለን።
በተመሳሳይ ዜና የአሜሪካ መንግሥት በአፍሪካ ሀገራት ላይ የጣለው የጉዞ ክልከላ ዲፕሎማሲያዊ ግኑኝነትን የሚያሻከር እንደሆነ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን መግለጹን ኢዜአ ዘግቧል።
የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን የአሜሪካ መንግሥት ያወጣው የጉዞ ክልከላ አዋጅን አስመልክቶ በሰጠው መግለጫ የአሜሪካ መንግሥት በተለያዩ ሀገራት በተለይም በአፍሪካ ሀገራት ላይ የጣለው የጉዞ ክልከላ ጉዳት የሚያስከትል መሆኑን አስታውቋል።
ማንኛውም ሀገር የዜጎቹን ደኅንነት እና የሀገሩን ሉዓላዊነት የማስጠበቅ መብት እንዳለው እናከብራለን ያለው ኮሚሽኑ፣ የክልከላ አዋጁ ሚዛናዊነትን ያልጠበቀ፣ ተዓማኒነትን እና ረጅም ዘመናትን ያስቆጠረው የአሜሪካ እና የአፍሪካ ግኑኝነትን የሚጎዳ መሆን የለበትም ብሏል።
የተመረጡ ሀገራት ዜጎች ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ ክልከላ የሚያደርገው አዋጅ የሁለቱን አህጉር ለዘመናት የተገነባ ዲፕሎማሲያዊ ግኑኝነት የሚያሻከር መሆኑንም ገልጿል።
አዋጁ የሕዝብ ለሕዝብ ግኑኝትን የሚጎዳ፣ በትምህርት እና ንግድ ልውውጥ ላይ ተፅዕኖ የሚያሳድር እንደሆነም ነው ያሳወቀው።
የአፍሪካ እና አሜሪካ በጋራ ፍላጎት ላይ የተመሠረተ ግኑኘነትን በማጠናከር ለዘላቂ ሰላም እና ብልጽግና እንዲሁም በትብብር ላይ መሠረት ያደረገ ዲፕሎማሲያዊ ግኑኝነት መኖሩን ኮሚሽኑ ያወጣው መግለጫ ያመልክታል።
አሁንም ቢሆን የአሜሪካ መንግሥት ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ሀገራት ጋር በንግግር ላይ የተመሠረተ እና አካታች የሆነ የመፍትሔ አማራጭ እንዲፈልግ ኮሚሽኑ ጠይቋል።
ኮሚሽኑ በአፍሪካ እና በአሜሪካ መካከል መግባባት የሚፈጠርበትን፣ ችግሮች የሚፈቱበትን እና ትብብርን የሚያጠናክሩ ጥረቶችን ለመደገፍ ዝግጁ መሆኑን ገልጿል።