ዛሬ ደም ውድ በሆነበት ጊዜ ላይ ሲስተር አሠጋሽ ጎሳ ደም በመለገስ የሴቶችን ክብረወሰን መያዛቸው ተሰማ። ሲስተር አሠጋሽ ጎሳ ለ80ኛ ጊዜ ደም በመለገስ በኢትዮጵያ የሴቶችን ክብረወሰን መያዛቸውን ያስታወቁት የጤና ሚኒስትር ዶክተር ሊያ ታደሰ ናቸው።

ዶክተር ሊያ በማህበራዊ ገጻቸው ላይ “ሲስተር አሠጋሽ ጎሳ ነርስም፣ እናትም ቀዳሚ ደም ለጋሽም በመሆን ዛሬ የሴቶች ቀንን በማስመልከት 80ኛ የደም ልገሣዋን አድርጋለች። ይህ ቁጥር በሃገራችን ሴት ደም ለጋሾች በክብረወሰን የተመዘገበ ነው” ሲሉ ነው ክብርም ምስጋናም ያቀረቡት።
በኢትዮጵያ መልካም ዜናዎችን የማጉላት ችግር ስር የሰደደ በሽታ መሆኑ እንጂ ሲስተር አሰጋሽ ያበረከቱት መልካም ተግባር የማህበራዊ አምዶችንና የዜና አውታሮችን ማደረስ የነበረበት ጉዳይ እንደነበር ዜናውን የሰሙ አስተያየት ሰጥተዋል። ለዚያውም በዛሬው ጊዜ።
ድህነታችንና ረሃብተኛ መሆናችን ማንም እየተነሳ የሚጋልብብን እንዳደረገን እየታወቀ በኢትዮጵያ ታሪክ ተደርጎ በማይታወቅ መልኩ ስንዴ ከውጭ ለማስገባት እቅድ ተያዞ በበጋ በሚሊዮን የሚቆጠር ስንዴ በመስኖ ሲመረት ያደነቀ የለም። ” ሉዓላዊነታችን የሚረጋገጠው በምግብ ራስን በመቻል ነው” እየተባለ ይህንኑ ለማድረግ የሚበረታታ ተግባር ሲፈጸም ቢያንስ አርሶ አደሩን አለማድነቅ ህመም ነው።
ሞት፣ ወደቀ፣ ገደለ፣ ተገደለ፣ ተቃጠለ … የሚሉ ዜናዎች ብቻ እንደ ሸቀጥ የሚሰራጭባት ኢትዮጵያ እንደ ሲስተር አሰጋሽ አይነቶችን ለጋስ፣ ለዛውም ደም ለ80ኛ ጊዜ የሰጡ ዜጋን አለማንገሱ ብዙም እንደማያስደንቅ ከምስላቸው በታች የተሰጡ አስተያየቶች ይመሰክራሉ።