“በዚህ ችግር ምክንያት ሰዎች የኮቪድ መከላከያ ክትባቶችን እንዳያገኙ፣ ሚሊዮኖች ለሞት እንዲዳረጉና ከግለሰቦች እጅ በልግስና የሚሰበሰበው ገንዘብ ከጥቅም ውጪ ሆኗል”
በዓለም ጤና ድርጅት ውስጥ እየጨመረ በመጣው የሥነ ምግባር ጉድለት፤ማጭበርበርና ጾታዊ ጥቃት የድርጅቱ ዳይሬክተር ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም ከሃላፊነታቸው እንዲነሱ ተጠይቋል።
የመከላከያ ሰራዊት መልቀቅ ተከትሎ ትህነግ መቀለ ሲገባ “ኩራት” በማለት በፌስ ቡክ አድናቆታቸውን የገለጹት ተኢዎድሮስ፣ የዓለም አቀፉ ገለልተኛ የፋይናንስ ተቋም (ኢንዲፔንደንት ፋይናንሽያል ኦዲት) ባቀረበው የኦዲት ሪፖርት በዓለም ጤና ድርጅት ውስጥ የሥነ ምግባር ጉድለት፣ ማጭበርበር፣ ጾታዊ ጥቃትና የሙያ ደረጃዎችን ያልጠበቁ አሰራሮች በከፍተኛ ሁኔታ መጨመሩን አመልክቷል።

የአለም ጤና ድርጅት እ.ኤ.አ የ2020 አመታዊ አፈጻጸምን በተመለከተ የኦዲት ሪፖርት ቀርቧል። በዚህም በተቋሙ እየጨመረ የመጣውን የሥነ ምግባር ጉድለት ማጭበርበርና ጾታዊ ጥቃት ተከትሎ የድርጅቱ ዳይሬክተር ለሁለተኛ ጊዜ እንዳይመረጡ የአለም ኤች አይቪ ኤድስ ሄልዚኬር ፋውንዴሽን ጠይቋል።
በሪፖርቱ መሰረት በ2020 የበጀት ዓመት የአለም ጤና ድርጅት ከ332 ሚሊዮን ዶላር በላይ ከአሰራር ውጪ ከአማካሪ ድርጅቶች ጋር ስምምነት ማድረጉን አመለክቷል። በተጨማሪም 2.5 ሚሊዮን ደላር ከደረጃ በታች በሆኑ ውሎች በመዋዋል ገንዘቡ ለኪሳራ የተዳረገ መሆኑንን ሪፖርቱ ይፋ አድርጓል።
ፋውንዴሽኑ በድርጅቱ ላይ ለታዩት ከፍተኛ ችግሮች ተጠያቂው ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም መሆናቸውን አመልክቶ ለሁለተኛ ዙር የድርጅቱ አመራርነት እንዳይመረጡ በማሳሰብ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጥያቄውን መረጃ አስደግፎ አስታውቋል።
የኦዲት ግኝቶቹ በዓለም የጤና ድርጅት ውስጥ እየተከናወኑ ያሉ የመልካም አስተዳደር ችግሮች እና በስራዎቹ ላይ ግልፅነት የጎደለው አሰራር መኖሩን እንደሚያመለክቱም አስታውቋል።
“በዚህ ችግር ምክንያት ሰዎች የኮቪድ መከላከያ ክትባቶችን እንዳያገኙ፣ ሚሊዮኖች ለሞት እንዲዳረጉና ከግለሰቦች እጅ በልግስና የሚሰበሰበው ገንዘብ ከጥቅም ውጪ ሆኗል” ሲሉ የኤች አይቪ ኤድስ ሄልዚኬር ፋውንዴሽን ፕሬዚዳንት ማይክል ዌንስተን ተናግረዋል።
የአለም ጤና ድርጅትን አመኔታ ለመመለስና የታዩ የመልካም አስተዳደርና ሌሎች ችግሮች ለመቅረፍ ተመድ አዲስ ፕሬዚዳንት ሊሾም እንደሚገባም ፕሬዚዳንቱ ማስታወቃቸውን ቢዝነስ ዋየር አስነብቧል። ENA.