በአፋር ክልል በኮሪና በጭፍራ ወረዳ በህገ ወጥ መንገድ ሲዘዋወር የተገኘ ከ13 ሚሊዮን ብር በላይ መያዙን የአውሳ ዞን ፖሊስ መምሪያ አስታውቋል።
በአውሳ ዞን በኮሪ ወረዳና በጭፍራ ወረዳ በኬላ ላይ በተደረገ ፍተሻ ከ13 ሚሊዮን ብር በላይ ተይዟል።
የአውሳ ዞን ፖሊስ መምሪያ አዛዥ ረዳት ኮሚሽነር አሃዶ መሀመድ እንደገለፁት በህገ ወጥ የገንዘብ ዝውውር አውሳ ዞን በኮሪ ወረዳና በጭፍራ ወረዳ ኬላ ላይ በተደረገ ፍተሻ 13 ሚሊዮን 53 ሺህ 490 ብር ተይዞ በምርመራ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
በሶስት ወራት ውስጥ ብቻ በህገ ወጥ ዝውውር 216 ኩንታል ጨው፣ በሚሌና በዱብቲ ወረዳዎች ቤንዚል ባለ25 ሊትር 80 ጀሪካንና ባለ2 ሊትር ሀይላንድ 280 መያዙን ገልፀዋል።

በተመሳሳይ በሌላ ጊዜም 24 በርሜል ናፍጣ/ነዳጅ እና ባለ 25 ሊትር 250 ጀሪካን እንዲሁም 50 ኩንታል ስኳር በህገ ወጥ መንገድ ሲዘዋወር ተገኝቶ በምርመራ ላይ እንደሚገኝ መናገራቸውን የክልሉ መንግስት ኮሙዩኒኬሽን መረጃ ያመለክታል። (ኢ ፕ ድ)