ከመሆኑም በላይ ሚዲያዎች እስከ አሁን ከመጡበት አካሄድ ለየት ባለ ሁኔታ የራሳቸውን እቅድ ይዘው መስራት አለባቸው።
ለምሳሌ የኢትዮጵያ ችግር ምንድን ነው? የቱስ ጋር ነው? የቱ ጋር ነው የተበላሸነው? ለምን ሰላም አጣን? ለምንድን ነው እዚህም እዚያም ሰዎች በጦርነት የሚያልቁት? ለምን መነጋገር አቃተን? ምንድነው ችግሩ? እያሉ እየሰሩ ግን ደግሞ ወደዋናው የምክክር መድረክ የሚመጣበትን መንገድ ሁሉም ቁጭ ብሎ የሚነጋገርበትን አውድ መፍጠር የሚጠበቅ ነው።
ምክንያቱም ዛሬ ጋዜጠኛ ሆነን የተለያየ ቦታ እንደልባችን ሄደን ዘገባ የምንሰራበት ወቅት ላይ አይደለንም፤ ይህ ሁኔታ በራሱ ሚዲያው የምክክሩ አካል እንዲሆን ያስገድደዋል፤ በመሆኑም እነዚህ ነገሮች ሁሉ ከግምት ውስጥ በማስገባት በጣም በጥልቀት ሰርቶ የምክክር ኮሚሽኑን የሶስት ዓመት የስራ እቅድ በቀሩት አስር ወራት ውስጥ ስኬታማ ማድረግ ይገባል።
የምክክር ኮሚሽኑ የተሰጠውን ጊዜ ሊያጠናቅቅ የቀረው 10 ወራት ብቻ ቢቀሩትም በአግባቡ ከተጠቀምንባቸው እነዚህ አስር ወራት ለኢትዮጵያውያን ወሳኝ ጊዜያት ናቸው ብሎ መውሰድ ይቻላል፡፡
ቀሪዎቹ አስር ወራት ከፍተኛ የሆነ ስራ የሚሰራባቸው ጊዜያት ናቸው። እስከ አሁን የነበረው ስራ ቢያንስ በምክክሩ የሚሳተፉ ሰዎችን የመለየት ነው። ይህ ሂደት በራሱ እስከ ወረዳና ቀበሌ ድረስ መውረድን የሚጠይቅ በመሆኑና ሁሉንም የሕብረተሰብ ክፍሎች ወደፊት ማምጣት ስለነበረብን ረዘም ያለ ጊዜን ወስዷል። ሌላው ፓርቲዎችን ወደዚህ ምክክር ማምጣቱ በጣም አስቸጋሪ ሆኖ ስለቆየ ኮሚሽኑ ሰፊ ጊዜን ወስዶበታል። ከዚህ በኋላ ያሉትን ጊዜ በአግባቡ ለመጠቀም ሁሉም ዜጋ ለብሔራዊ ምክክሩ ትኩረት ሊሰጥ ይገባል፡፡
አዲስ ዘመን፡- በቀሪዎቹ ጊዜያት ከእያንዳንዱ ዜጋ ምን ይጠበቃል ?
አቶ ጥበቡ በለጠ፡- ኋላ ቀሩ የፖለቲካ ባህላችን በርካታ ችግሮችን አስከትሎብናል። ከመነጋገር ይልቅ በር ዘግቶ መወቃቀስና አልፎ ተርፎም ነፍጥ እስከማንሳትና መገዳደል ድረስ አድርሶናል። አሁን ኢትዮጵያ የሚያስፈልጋት ግጭት፤ ጦርነትና መወነጃጀል ሳይሆን ውይይትና ምክክር ብቻ ነው።
ስለዚህም ችግሮችን በውይይት የመፍታት ባሕልም እንደሀገር ሊጎለብት ይገባል። የስልጣኔም አንዱ መለኪያም ይኸው ነውና። በኢትዮጵያ የፓርቲ ፖለቲካ ሥራ ውስጥም ሆነ በሌሎች መስኮች የተሰማሩ ወገኖች፣ ለውይይት ቅድሚያ መስጠት አለባቸው። ሀገራዊ ምክክሩን እንደ ዕድል ሊጠቀሙበት ይገባል፡፡
እንደ ሕዝብም የታሪካችን አንዱ ክፋይ ሆኖ ዘመናትን የተሻገረውን ጦርነትና ግጭትን ለማስወገድና የተረጋጋች፤ ሰላሟ የተጠበቀ እና የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመጭው ትውልድ ለማውረስ ሀገራዊ ምክክሩ ይዞ የመጣውን ዕድል መጠቀም ሀገርን የማሻገር አንዱ ተልኮ ነው፡፡ ስለዚህም በየትኛውም ጫፍ ያለ ኢትዮጵያዊ በዚህ የምክክር ሂደት መሳተፍና የመፍትሄው አካል መሆን ሀገርን ማዳን መሆኑን ሊረዳ ይገባል።
አካታች አገራዊ ምክክሮችን ማድረግ የተሻለ አገራዊ መግባባትን ይፈጥራል። ኢትዮጵያውያን በዘር፤ በሃይማኖት፤ በጾታና በአካባቢያዊ ርቀት ሳይገደቡ ስለሀገራቸው መጻኢ ዕድል ሊመክሩ ይገባል፡፡ ብሄራዊ ምክክሩ ከሞላ ጎደል ሁሉም ሃሳብ አለኝ የሚል የሕብረተሰብ ክፍል ሃሳቡን ያለምን ገደብ የሚሰጥበትና በመደማመጥ ጉዳዮች እልባት የሚያገኙበት ይሆናል የሚል ተስፋ መጨበጥ አለብን።
እፀገነት አክሊሉ አዲስ ዘመን