አንጋፋውን እና በኢትዮጵያ የመጀመርያ የሆነውን የያሬድ የሙዚቃ ትምህርት ቤትን የመስረቱ እና የመጀመሪያው ዳይሬከተር ሆነው ያገለገሉ፤ እንዲሁም በኢትዮጵያ የዘመናዊ ሙዚቃ እድገት ውስጥ ብርሀን ፈንጣቂ በመሆን የተለያዩ ዘመን አይሽሬ የሙዚቃ ስራዎችን ያበረከቱ፤ ለዘመናዊ የሙዚቃ እድገት አሻራቸውን ያሳረፉ ዕውቅ ፕሮፌሰር ናቸው ሲሉ የሙያው ምሁራን ይናገራሉ።
ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ “የኢትዮጵያ የሙዚቃ አቀናባሪ” እስከመባል የደረሱ በዚህም የተነሳ በ1959 ዓ.ም. የቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ በጎ አድራጎት ድርጅት ሽልማትን የተቀዳጁ ስመጥር ባለሙያ እንደሆኑም ይገልጻሉ ምሁራኑ፡፡
“ባላ ዋሽንቱ እረኛ” ወይም “The Shepherd Flutist” የተሰኘው ስራቸው በሀገራችን ኢትዮጵያ በስፋት ይታወቃል፡፡ በተጨማሪም ፕሮፌሰሩ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ1982 ደግሞ “Roots of Black Music” የተሰኘ መጽሐፍ ለህትመት አብቅተዋል፡፡
ከሀገራችን የሙዚቃ እድገት አስተዋጿቸው ባሻገር በጎረቤት ሀገር ሱዳን የዳንስና ደራማ ኢንስቲትዩት በማቋቋም ላበረከቱት ጉልህ አበርክቶ ከተባበሩት መንግስታት የትምህርት፤ የሳይንስና ባህል ተቋም ከፍተኛ እውቅናን ማግኘት መቻላቸውን ታሪካቸው ያሳያል፡፡
እልፍ የዘመናዊ ሙዚቃ ስራዎችን ያበረከቱት ፕሮፌሰር አሸናፊ በአሜሪካ፤ ካናዳና በተለያዩ የአውሮፓ ሀገራት ስራዎቻቸውን በማቅረብ አንቱታን ማትረፍ ከመቻላቸው ባሻገር ገና በ26 አመታቸው በሀንጋሪ ርዕሰ መዲና በሆነቸው ቡዳፔስት አስደማመሚ የሙዚቃ ኦርኬስትራን አስመልክተዋል፡፡ አሜሪካ በነበራቸው ቆይታ ከመኖሪያቸው ፍሎሪዳ ባሻገር በተለያዩ ግዛቶች በመዘዋወር የሙዚቃ እውቀታቸውን ለትውልድ ማጋራታቸው ይጠቀሳል፡፡
በ1960ዎቹ ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ በተከታታይ የማስትሬትና የፒ.ኤች.ዲ ትምህርታቸውን ማሳካታቸው እንዲሁም በዘመናቸው የተለያዩ ጥናታዊ ፅሁፎችን ለዓለም ማበርከታቸው ከብዙ በጥቂቱ ይታወሳል፡፡