የፊንጢጣ ኪንታሮት በአንጀት የመጨረሻው ክፍል እና ፊንጢጣ አካባቢ የሚከሰት ህመም ነው። ይህም በሴቶችም በወንዶችም ላይ የሚያጋጥም ሲሆን፣ በተለይ ሴቶች በእርግዝና ወቅት እና በወሊድ ጊዜ ሊያጋጥማቸው ይችላል።
እንደ ጆንስ ሆፕኪንስ መረጃ ከሆነ ግማሽ ያህል የሚሆነው የዓለም ሕዝብ በ50 ዓመቱ ይህ በሽታ ያጋጥመዋል።
በኢትዮጵያ ምን ያህል ሰዎች የዚህ በሽታ ተጠቂ እንደሆኑ የሚያሳይ ጥናት ባይኖርም፣ በተለይ ረዥም ጊዜ በመቀመጥ የሚያሳልፉ፣ ብዙ ጊዜ የሆድ ድርቀት እንዲሁም ተቅማጥ የሚያጋጥማቸው ሰዎች ላይ በብዛት እንደሚታይ ባለሙያዎች ይናገራሉ።
በባህል፣ በማኅበራዊ እና ግላዊ በሆኑ ምክንያቶች ችግሩ ሳይባባስ ወደ ሕክምና ተቋም የመሄድ ፍላጎትም አነስተኛ እንደሆነ ይነገራል።
ለመሆኑ በፊንጢጣ አካባቢ የሚታይ እብጠት እና ህመም ሁሉ ኪንታሮት ነው? ሕክምና የሚያስፈልገውስ መቼ ነው? ካልታከመስ ምን ያስከትላል? ከፊንጢጣ ካንሰርስ የሚለየው በምንድን ነው?
ዶ/ር ሰለሞን በቀለ ለእነዚህ ጥያቄዎች ምላሽ አላቸው
ዶ/ር ሰለሞን በቀለ የአንጀት እና የፊንጢጣ ከፍተኛ ቀዶ ሕክምና (ኮሎሬክታል ሰርጀሪ) ስፔሻሊስት ናቸው። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በረዳት ፕሮፌሰርነት የቀዶ ሕክምና ባለሙያ ሲሆኑ፣ በላንሴት ሆስፒታልም በቀዶ ሕክምና ክፍል ይሠራሉ።
ዶ/ር ሰለሞን በእንግሊዝኛ አጠራሩ ሄሞሮይድስ ወይም ኪንታሮት፣በፊንጢጣ አካባቢ ባሉ ኅብረ ህዋሳት (ቲሹ) ላይ የሚያጋጥም የጤና እክል ነው ይላሉ።
እነዚህ ህዋሳት ሄሞሮይድስ የሚባሉ ሲሆን፣ ስንፈጠር አብረውን የሚፈጠሩ ናቸው። የሰገራ መቆጣጠሪያ ጡንቻን በመርዳትም የፊንጢጣ ሥራን ያግዛሉ።
ታዲያ እነዚህን ቲሹዎች የሚገፋቸው፣ ካሉበት ቦታ እንዲንቀሳቀሱ የሚያደርጋቸው አሊያም በሰበቃ (ፍሪክሽን) ምክንያት የሚፍቋቸው ነገሮች ሲያጋጥማቸው እክል ይገጥማቸዋል።ይህም መድማት ወይም እብጠት ሲያስከትል ሄሞሮይድ (ኪንታሮት) ተከሰተ እንደሚባል ባለሙያው ያስረዳሉ።
ሆኖም በፊንጢጣ አካባቢ የሚወጣ ያልተለመደ ነገር ሁሉ ኪንታሮት አይደለም።
ዶ/ር ሰለሞን እንደሚሉት በፊንጢጣ አካባቢ እብጠት ብቻም ሆነ ፈሳሽ የሚያመጣ እብጠት፣ ትርፍ ቆዳ (ስኪን ታግ)፣ የፊንጢጣ ካንሰር እንዲሁም ፊስቱላ ሊከሰት ይችላል።
ፊንጢጣ አካባቢ ኢንፌክሽን ካጋጠመ በኋላም የመግል መጠራቀም (አናል አብሰስ) የሚከሰትበት አጋጣሚ ይኖራል።
ከእነዚህም በተጨማሪ የአንጀት የመጨረሻው ክፍል ካንሰር እንዲሁም የፊንጢጣ ፊስቱላ (አናል ፊስቱላ) የሚያጋጥማቸውም ሰዎች አሉ።ፊስቱላ በሰገራ መውጫ እና በቆዳው መካከል ስንጥቃት ሲኖር የሚከሰት ነው።
ኪንታሮት ግን ከእነዚህ የተለየ ነው።
ኪንታሮት በፊንጢጣ አካባቢ የሚገኘው እና በውስጡ እንደ ደም ሥር ያሉ የተለያዩ ሥሮች የያዘው የሰውነት አካል (ቲሹ) በተለያየ ምክንያት ሲያብጥ እና መድማት ሲያስከትል የሚያጋጥም ነው።
ኪንታሮትን ተቀራራቢ ምልክት ካላቸው ሌሎች በሽታዎች በቀላሉ መለየት እንደሚቻልም ዶ/ር ሰለሞን ያስረዳሉ።
“ምንም ህመም የሌለው መድማት ካለ፣ ሰገራ ከወጣ በኋላ ደም የሚወጣ ከሆነ እንዲሁም ሰገራ በሚወጣበት ጊዜ በፊንጢጣ አካባቢ ከውስጥ የሚወጣ አሊያም ወጥቶ የማይመለስ እብጠት ሲኖር ኪንታሮት የመሆን ዕድሉ ከፍተኛ ነው” ይላሉ።
ምንም እንኳን ምልክቶቹ እንደ በሽታው ደረጃ እና እንደ የኪንታሮቱ ዓይነት የሚለያይ ቢሆንም በዋናነት ምልክቶቹን በማስተዋል ከሌሎቹ ህመሞች መለየት እንደሚቻል ባለሙያው ያስረዳሉ።
የፊንጢጣ ኪንታሮት እና የፊንጢጣ ካንሰር
በአንዳንድ ሰዎች ዘንድ ኪንታሮት ወደ ካንሰር ይቀየራል የሚል አሊያም በዚያ አካባቢ የሚከሰተውን የጤና እክል ሁሉ ካንሰር ነው የሚል አስተሳሰብ አለ። በመሆኑም እዚህ ላይ ስለ ፊንጢጣ ካንሰር ጥቂት ማለት ያሻል።
ዶ/ር ሰለሞን እንደሚያስረዱት የፊንጢጣ ካንሰርም ሆነ ኪንታሮት እብጠትን ያስከትላሉ። ሆኖም የፊንጢጣ ካንሰር እባጩ ጠጠር ያለ፣ ጠንካራ እና ከቀን ወደ ቀን እየጨመረ የሚሄድ ሲሆን የኪንታሮት በሽታ ደግሞ የሚያብጠው ክፍል እንደ ፊንጢጣ ቆዳ ለስላሳ ነው።
ሌላው የሚለያቸው ነገር ኪንታሮት ገባ ወጣ የሚል ሲሆን፣ ካንሰር ግን እዚያው የወጣበት ቦታ ላይ እየጨመረ የሚመጣ እብጠትን ያስከትላል።
ሆኖም አንድ ሰው ያጋጠመውን ህመም ለመለየት በጤና ባለሙያ መታየት እንዳለበት ዶ/ር ሰለሞን ይመክራሉ።
የኪንታሮት ዓይነቶች
ዶ/ር ሰለሞን ኪንታሮት በሚከሰትበት ቦታ በሁለት እንደሚከፈል ያስረዳሉ። አንደኛው በውስጥ ሌላኛው ደግሞ በውጭ የሚከሰት ነው።
የውስጥ (Internal haemorrhoids) የሚባለው ከውጭ የማይታይ ግን ከፊንጢጣ ቆዳው ሁለት ሴንቲሜትር ገባ ብሎ የሚከሰት ነው። ይህ ኪንታሮት በሚያብጥ ጊዜ በመጠኑ ትልቅ ከሆነ ወደ ውጭ ይወጣል። ካልሆነ ደግሞ ውስጥ ሆኖ የሚደማ ይሆናል።
የውጭ ኪንታሮት (External haemorrhoids) ደግሞ ቆዳው ላይ ያለ እና ቆዳው ላይ አብጦ፣ አንዳንዴ መድማት አንዳንዴ ህመም፣ አንዳንዴ ደግሞ ሄድ መጣ የሚል እብጠት የሚያስከትል ነው።
ይህ ዓይነቱ ኪንታሮት ከውስጥ ጀምሮ ወደ ውጭ ወጣ ገባ የሚል ነው፤ ነገር ግን ከፊንጢጣው አሊያም ከክቡ የፊንጢጣው ክፍል ወጣ ብሎ ወደ ጎን ወዳለው ቆዳ የሚሄድ እብጠትን አያመጣም።
በተደጋጋሚ ተቅማጥ የሚያጋጥማቸው ሰዎች፣ የሆድ ድርቀት ያለበት እና ረጅም ጊዜ የሚቀመጡ ሰዎች፣ ከልክ በላይ ክብደት ያላቸው እንዲሁም በተለይ በሴቶች ዘንድ ደግሞ በእርግዝና ወቅት ኪንታሮት ሊያጋጥም እንደሚችል ዶ/ር ሰለሞን ያስረዳሉ።
ረዥም ሰዓት የሚቀመጡ ሰዎች፣ ሹፌሮች፣ ሴቶች (በእርግዝና ወቅት)፣ ስልክ ይዘው ወይም በሌላ ሰበብ ረዥም ሰዓት ሽንት ቤት የሚቀመጡ ሰዎች ይበልጥ ለበሽታው ተጋላጭ ናቸው።
ሴቶች በእርግዝና እና በወሊድ ወቅት ማለትም ፅንስ መሸከም በደም ሥሮች ላይ በሚፈጥረው ጫና እንዲሁም በምጥ ወቅት ተጨማሪ ግፊት ስለሚኖር ለኪንታሮት የመጋለጥ ዕድላቸው ሰፊ ነው።
ማኅበራዊ ሚዲያ እና ኪንታሮት
እንደ ግሎባል ዲጂታል ኢንሳይት ከሆነ አንድ ሰው በአማካይ በቀን ውስጥ ሁለት ሰዓት ተኩል ማኅበራዊ ሚዲያ በመጠቀም ያጠፋል። ሰዎች ማኅበራዊ ሚዲያ ከሚጠቀሙባቸው ቦታዎች አንዱ ደግሞ መጸዳጃ ቤት ነው።
ምንም እንኳን ማኅበራዊ ሚዲያ እና ኪንታሮትን በተለየ የተመለከቱ ጥናቶች ባይኖሩም፣ ቢሮም ውስጥ ሆነ ሽንት ቤት ውስጥ ለረጅም ጊዜ መቀመጥ ለፊንጢጣ ኪንታሮት ከሚዳርጉ መንስኤዎች አንዱ ነው። በመሆኑም በዚህም ምክንያት ማኅበራዊ ሚዲያም ተመሳሳይ ተፅዕኖ ያስከትላል ማለት ነው።
ዶ/ር ሰለሞን እንደሚሉት በርካታ ሰዎች ኪንታሮት ይኖራቸዋል። ሕይወታቸው እስከሚያልፍ ድረስም አብሯቸው ይቆያል።
በአብዛኛው ለዚህ ህመም የተዳረጉ ሰዎች ምን እንደሚያባብስባቸው ካወቁና የአኗኗር ዘይቤያቸውን ካስተካከሉ ከበሽታው ጋር አብሮ መኖር እንደሚቻል ባለሙያው ይናገራሉ።
እንደ ፓስታ፣ ቅባት የበዛው፣ መኮሮኒ ዳቦ እና አሰር (ፋይበር) የሌላቸው ሰገራን የሚያደርቁ ምግቦችን ባለመመገብ እና አካላዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ህመሙን ሊከላከሉ ይችላሉ።
ነገር ግን የተወሰኑ ሰዎች ላይ ኪንታሮት ውስብስብ የጤና ችግር ሊያስከትል ስለሚችል እንደየደረጃው ሕክምና እንደሚያስፈልግ ባለሙያው ይመክራሉ።
የውስጥ ኪንታሮት አራት ደረጃዎች ያሉት ሲሆን፣ በየደረጃው ከቀላል እስከ ከባድ ሕክምና ያስፈልገዋል።
- አንደኛ ደረጃ፡ ምንም እብጠት የሌለው እና ህመም የሌለው መድማት
- ሁለተኛ ደረጃ፡ እብጠት ኖሮ፣ ሽንት ቤት ከተፀዳዱ በኋላ የሚመለስ
- ሦስተኛ ደረጃ፡ እብጠት ኖሮ ታማሚው በእጁ ካልመለሰው በስተቀር ወደ ውስጥ የማይገባ እብጠት
- አራተኛ ደረጃ ፡ ውጭ ላይ የሚቆይ እብጠት፣
በመሆኑም አንድ ሰው በተለይ ሦስተኛ እና አራተኛ ደረጃ ላይ የደርሰ ኪንታሮት ካጋጠመው እና በሌሎቹም የህመም ደረጃዎች ተደጋጋሚ ደም መፍሰስ እና የዕለት ተዕለት ሕይወቱ ላይ ተፅዕኖ ካሳደረ ሕክምና እንደሚያስፈልገው ባለሙያው ያስረዳሉ።
ሕክምናዎቹ ምንድን ናቸው?
ኪንታሮት በደረጃ የሚሰጥ ሕክምና ነው ያለው ይላሉ ዶ/ር ሰለሞን። እንደ ዓይነቶቹም ይለያያል።
የውጭ ኪንታሮት ከሆነ ምልክቱ እብጠት እና ህመም እንዲሁም አንዳንድ ጊዜ መድማት በሚከሰትበት ጊዜ ህመሙ እንዲጠፋ የሚያደርግ ማስታገሻ በመውሰድ፣ ለብ ያለ ውሃ ላይ ትንሽ ጨው አድርጎ በመዘፍዘፍ፣ ሰገራ ማለስለሻ መድኃኒት እና ምግቦችን በመመገብ ማስታገስ ይቻላል።
በዚህም እብጠቱ እስከሚሟሽሽ እስከ ሁለት ሳምንት ጊዜ ሊወስድ ይችላል። የተወሰኑ ሰዎች ህመሙ ካስቸገራቸው ኪንታሮቱ የቋጠረውን ደም ማስተንፈስ አማራጭ የሚሆንበት ጊዜ አለ።
የውስጥ ኪንታሮት ሲሆን ደግሞ ሕክምናው በደረጃው ይወሰናል። የሚደማ ከሆነ እና እብጠት ከሌለው እንዳይደማ የሚያደርግ መድኃኒት በመስጠት፣ ብዙ ፈሳሽ መጠጣት፣ አመጋገብን ማስተካከል እና የአካል እንቅስቃሴ ማድረግ ይመከራል።
አንዳንድ ሰዎች ላይ መድማቱ የማይቆም እና በብዛት የሚደማ ከሆነ የሚደማውን ቦታ ማሰር አሊያም መቋጠር ያስፈልጋል። ሁለተኛ ደረጃም ማለትም እያበጠ እየወጣ የሚያስቸግራቸው ከሆነም ተመሳሳይ ሕክምና ይደረጋል።
ሆኖም በተደጋጋሚ የሚያስቸግራቸው ከሆነ ግን እብጠቱን ሥሩ ላይ ገብቶ ማሰር አሊያም በአልትራ ሳውንድ በመታገዝ ሄሞሮይዱን ያሳበጠውን የደም ሥር ማሰር እና መቋጠር አንዳንዴም መቁረጥ ሊያስፈልግ ይችላል።
ሦስተኛ እና አራተኛ ደረጃ የውስጥ ኪንታሮት ካጋጠመም መቆረጥ ሊያስፈልገው ይችላል። ይህ ብዙ ሰዎች ላይ ውጤታማ ሲሆን ሄሞሮይድን የማጥፋት ዕድሉም ከፍተኛ ነው።
ባህላዊ ሕክምናስ?
የባህል ሕክምና አዋቂዎች ፍቱን መድኃኒት እንዳላቸው ከሚጠቅሱላቸው በሽታዎች ዝርዝር ውስጥ ኪንታሮት ይገኝበታል። አንዳንድ ሰዎችም በባህል ሕክምና ኪንታሮት አስወጣሁ፣ ጠፋልኝ ሲሉ ይሰማል።
ዶ/ር ሰለሞን እንደሚሉትም 70 በመቶ ገደማ የሚሆኑ ሰዎች ወደ ጤና ባለሙያ ከመሄዳቸው በፊት የባህል ሕክምናን ይሞክራሉ አሊያም የባህል ሐኪም ምክር ይሰማሉ።
ሆኖም ባህላዊ ሕክምና አድርገው ውስብስብ የጤና ችግር አጋጥሟቸው ወደ ሕክምና ተቋም የሚመጡ እንዳሉ ዶ/ር ሰለሞን ይናገራሉ።
ኪንታሮት የአኗኗር እና የአመጋገብ ዘይቤን ማስተካከል ከተቻለ ተከባብሮ መኖር ይቻላል የሚሉት ባለሙያው፤ በዚህ መስተካከል ካልቻለ ግን ወደ ባህል ሕክምና መሄድ ሳይሆን የሕክምና ባለሙያ ማማከር እንደሚገባ ይመክራሉ።

ከኪንታሮት ጋር ተያይዞ የሚነሱ የተሳሳቱ አመለካከቶች
- የፊንጢጣ ኪንታሮት ነቀርሳ ወይም ካንሰር ነው – ዶ/ር ሰለሞን እንደሚሉት የፊንጢጣ ኪንታሮት ወደ ምንም ሊቀየር አይችልም። እንደ ደረጃው በወቅቱ ከታከመ ሕይወትን አደጋ ላይ የሚጥል ነገር አይደለም።
- ሁሉም የፊንጢጣ ኪንታሮት መታከም አለበት – ሁሉም ኪንታሮት ቀዶ ሕክምና አሊያም ባህላዊ ሕክምና አያስፈልገውም። አመጋገብን፣ የአኗኗር ዘይቤን ማስተካከል እና የሚያባብሰውን ነገር ማስወገድ እስከተቻለ ድረስ ከኪንታሮት ጋር ተስማምቶ መኖር ይቻላል።
- ቀዶ ሕክምና ከተደረገ ፊንጢጣው ችግር ይደርስበታል – በቀዶ ሕክምና ምክንያት የፊንጢጣው ቀለበት ይጠባል፤ ውስብስብ የጤና ችግር ያስከትላል የሚል አመለካከት አለ።ይህም ወደ ባህል ሕክምና እንዲሄዱ ወይም እየተሰቃዩም ቢሆን ይዘውት ቁጭ እንዲሉ ያደርጋል። ሆኖም ሁሉም ቀዶ ሕክምና የራሱ የሆኑ ተጓዳኝ ችግሮች ቢኖሩትም እነዚያን ችግሮች እንዳይከሰቱ ማድረግ ይቻላል። በመሆኑም ሕክምና ከማድረግ መታቀብ እንደሌለባቸው ባለሙያው ይመክራሉ።
- ቀዶ ሕክምና ከተደረገ በኋላ መልሶ ይተካል – አንዳንድ ሰው ኪንታሮት መልሶ ይተካል ይላል። ሆኖም ሄምሮይድ በፊንጢጣ ዙሪያ እና በውስጡ ያለ የአካል ክፍል ነው። በአብዛኛው ቲሹው በፊንጢጣ ሦስት ቦታ ነው ያለው። ለምሳሌ በቀኝ በኩል ያለው አብጦ ከነበረና ተቆርጦ ከወጣ በኋላ እዚያው ቦታ ላይ መልሶ አይወጣም። ሆኖም መንስኤዎቹን ማስወገድ ካልተቻለ በሌላ በኩል ያለው ቲሹ ሊያብጥ ይችላል። ቀዶ ሕክምና መልሶ የመተካት ዕድሉ አነስተኛ ነው።
- ኪንታሮት የወገብ ህመም ያመጣል – ረጅም ሰዓት መቀመጥ ለፊንጢጣ ኪንታሮት እንደሚዳርገው ሁሉ የወገብ ህመምም መንስኤ ነው። በመሆኑም የአንጀት ድርቀት ያለባቸው ሰዎችም ለመጸዳዳት ረጅም ጊዜ ስለሚቀመጡ ጀርባቸውን ሊያማቸው ይችላል። ከዚያ ውጪ ግን ከጀርባ ህመም ጋር በቀጥታ አይገናኝም።
ምስጋና ለቢቢሲ አማርኛ