“ኦሮሞን /ኩሽ/ የጋራ ጠላት አድርገን መንግስት እንገልብጥ ” የሚል ጥቅል አሳብ ያለው የኢሳያስ ዲስኩር መሰማቱን ተከትሎ ይፋ የሚወጡ መረጃዎች እንደሚያስረዱት፣ የቀድሞ አምባሳደር ብርሃነ ገብረክርስቶስን ጨምሮ ሌሎች የትህነግ ወታደራዊ መኮንኖችና የፋኖ ወኪሎች አስመራ ነበሩ። አሁን ድረስም እዛው የሚገኙ መኖራቸውም ታውቋል። “ሰሜኖቹ” የሚል ታቤላ የተለጠፈለት አዲሱን የዕልቂት ድግስ አስመራ ላይ ሲቦካ ስንቅና ነዳጅ ይሆነው ዘንዳ የፈጠራ ትርክትና በሰነድ የተደገፈ ሴራ እንዲመረት አቅጣጫ የተሰጠው።
“ፖለቲከኞች፣ አክቲቪስት ነን የሚሉ፣ ድርጅቶች፣ ራሳቸው የሚዲያ ግሩፖችና ባለቤቶች ወዘተ ቁጭ ብለው የፈጠራ ሰነድ፣ ትርክት፣ ዶክመንታሪ ወይም ሪፖርትና ሰበር ዜና የሚሆን ወሬ ያመርታሉ። ኢትዮ360 ከሚያሰራጨው ዜና ዘጠና ከመቶው የሃሰት እንደነበር ባልደረባቸው አጋልጧል። ሶስት ሟቾችንና አንድ ገዳይን ደምሮ አራቱንም በማጀገን የቅጥፈት ትርክት ተሰርቶ ተሽጧል። በኢትዮጵያ ስም እየቀየሩና እየፈጠሩ ሰነድ አዘጋጅቶ አንድን ህዝብ፣ ወገን፣ ብሄር፣ ባለስልጣን በማራከስ በሕዝብ እንዲጠላ ማድረግ ብዙም አያስቸግርም” የምስክሮች ቃል ነው።
በሴራ አገር እስከማፍረስ ተደርሶ ነበር። በቅጥፈትና በቅጥፈት መረጃ “ወሬ የፈታው” እስኪባል ተደርሶ ነበር። በፈጠራ ዜናና የሰበር ወሬ ጋጋታ የሚያዘውና የሚጨበጠው እስኪጠፋን ተተራምሰን ነበር። በደቦ የሚዲያ ነውጥ፣ የማህበራዊ አውድ ግልቢያ ወላልቀን ነበር። የትናንት የሃሰትና ቅጥፈት ፕሮፓጋንዳ አዝማቾች ወደ ቀልባቸው ተመልሰው የነገሩን ይህንኑ ነው። ይህንኑ የከሰርንበትን፣ በሚሊዮኖች የከሰርነበትን ጦርነት ውናው ሂሳብ አወራራጅ ሻዕቢያ ማሊያ ቀይሮ ዳግም ሊጋልብበት ነው። የተሸጡ፣ የከዱ፣ ዲቃላዎች አገራቸውን ሊያውኩና ለታሪካዊ ጠላቶቿ ለማስረከብ ዋናውን የባንዳ አሰማሪ ደጅ ጠንተዋል። ይህንኑ የሚያረጋግጥ መረጃ እየወጣ ነው።
ለበርካቶች እልቂት፣ አካል መጉደል፣መፈናቀል፣ መደፈር፣ ዝርፊያ፣ ንብረትና መሰረተ ልማት ውድመት እንዲሁም ለጥቅል ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ምክንያት የሆነው ጦርነት የሃሰት መረጃና ቅሰቀሳ ዋንኛ ነዳጁ ነበር። ያለ ምንም እውነታ ወይም በትንሽ ፍንጭ ላይ እየተተከለ ሲመረት የነበረው የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ አስከፊ ጉዳት ቢያደርስም አሁንም ድረስ ትምህርት የተወሰደ አይመስልም። በየአቅጣጫው የሚሰራጨውና የሚረጨው ቅስቀሳ አሁን ላይ ማረፊያውን “ሰሜኖችና ደቡቦች፣ ኩሽና ሴም ” በሚል እስከማቧደን ደርሷል።
ኤርትራ የተገነጠለችበትን ቀን አስመልክቶ ያለወትሯቸው በጤና ዕክል ሳቢያ የሃያ ደቂቃ አጭር ዲስኩር የደሰኮሩት ፕሬዚዳንት ኢሳያስ በግልጽ እንዳሉት መንግስትን “ኦሮሙማ” እሳቸው የቀረርጹትን አዲሱን የኃይል አሰላለፉ ደግሞ ” ሰሜኖችና ደቡቦች/ ኩሽና ሴም” በማለት ይፋ አድርገዋል። ይህንኑ ተከትሎ ዕቅዱን እንዲያሰርጹ በተለይ ” የተሸጡ” የሚባሉትን አማርኛ ተናጋሪዎችና “የዘሬ ያንዘርዝረኝ” ለሚሉት የቁጩ ኢትዮጵያዊነትን ለተከናነቡ መመሪያ መዘጋጀቱ ተሰምቷል።
ዲጂታል ወያኔን የሚመሩት የቀድሞው የስለላ ማሽን አቶ ጌታቸው አሰፋን ጭምሮ አስመራ ያሉት የትህነግ ተላላኪዎች ሃሰትን እውነት አስመስለው በሚያቀርቡ የቅብ “ኢትዮጵያዊያን” አማካይነት ሕዝብ ላይ እንዲደፋ የሚዘጋጁት ሰነዶች በተለይም “የሰሜናውያንና ኩሻውያን አዲስ አስተምሮት ኢሳያስን” የሚያጎሉ ናቸው። መረጃው ያላቸው እንደሚሉት ” በግል ጠባቂዎቻቸው ተሰረቀ” በተባለው የዶክተር ደብረጽዮን ኮምፒውተር ውስጥ የተገኘ ይሁን በሌላ ሳይብራሩ ዝርዝር ጉዳዮቹ መታወቃቸውን ገልጸዋል።
በዕቅዱ መሰረት ኑሮ ውድነቱን ወደ አመጽ ለመቀየር የተያዘው ሩጫና የሚዲያ ይቅብብሎሽ፣ የኢትዮጵያና የፋይናንስ ተቋማትን የማኮሰስ፣ የተሰሩ የልማት ስራዎችን ወደ ቅንጦትና ግለሰቦች ፍላጎት በመጎተት ሕዝብ ምሬት ውስጥ እንዲገባ የመቀስቀሱ ስራ እንዳለ ሆኖ፣ ኢሳያስ የነደፉትን አዲስ አሰላለፍ በሰነዶች የመደገፍ ዕቅድ ተይዟል።
ለመረጃው ቅርብ የሆኑ እንዳሉት ቀደም ሲል “የአዳማው ስብሰባ ሚስጢር፣ የጅማው ስብሰባ አፈትላኪ ሰነድ …” ወዘተ በሚል እነደተዘጋጁት ዓይነት መረጃዎች በዝግጅት ላይ ናቸው።
ሰሞኑን ከንግድ ባንክ ገንዘብ ለመስረቅ ሙከራ መደረጉንና ለማንቀሳቀስ የተሞከረው ገንዘብ ከሰባት ቢሊዮን ብር በላይ በመሆኑ ወዲያው መክሸፉን፣ በዚሁ ወንጀል ተባባሪ የሆኑ ተይዘው በምርመራ ላይ እንደሚገኙ እየታወቀ፣ ከዜናው ትንሽ እውነት በመያዝ መረጃውም “ኦሮሞ ባለሃብቶች፣ ባለጊዜውች፣ ኦሮሞ ባለስልጣኖች፣ ኦሮሞ ኢንቨስተሮች በፅር ዘረፉ” በሚል ስም ሳይቀር እየተጠቀሰ ሕዝብ ምሬት ውስጥ እንዲገባ፣ በዘር እንዲቧደን የማነሳሳት ስራ መሰራቱን የሚገልጹት ክፍሎች፣ ” እየተዘጋጀ ያለው ሰነድና ‘አፈትልኮ ከብልጸና’ እጅ የወጣ በሚል ለሕዝብ ሊሰራጭ የታቀደው መረጃ ተመሳሳይ ይዘት ያለው ነው” ብለዋል።
ቀደም ሲል “የአዳማው ስብሰባ ሰነድ እጃችን ገባ” በሚል፣ በቅርቡ ደግሞ ” የጅማው ቤተመንግስት ስብሰባ ሚስጢር ሰነድ” በማለት በተወሰኑ ቡድኖች ተዘጋጅቶ የተበተነውን የሃሰት ሰነድ እንደ ምሳሌ ያነሱት የዜናው ሰዎች፣ ዘመቻው በጥቅል ኦሮሞ ጠል ሆኖ የሚዘጋጅ እንደሆነ ጠቁመዋል።
“ሰሜኖቹ” በሚል አቶ ኢሳያስ በጭንቀት ያዋለዱት መቀናጆ፣ አዲስ ለፈጠረው የኩሽና ሴም ትርክት ማዳበሪያ እንዲሆኑ ታስበው የሚዘጋጁት የፈጠራ ሰነዶች አስመልክቶ ልምዳቸውን ያካፈሉ ለዝግጅት ክፋሉ ሃሳብ አጋርተዋል።
በሳቢና ጎታች ስልት አንዱ አቀባይ፣ ሌላኛው ገፊ እየሆኑ በሚያንቀሳቅሱት የፍጅት ዕቅድ ከሚያተኩርባቸው መንገዶች አንዱ በኃይማኖት ውስጥ ገብቶ የዘር እሳት ለማፋፋም የሚሆን ግብዓት ማዘጋጀት ነው። ለዚህም በዋናነት የሰሞኑን ምርጫ መጠቀም፣ ለዚህም የሚሆኑ ቃለ ምልልስ የሚሰጡና አጀንዳ የሚተክሉ ተዘጋጅተዋል።
በደንቢዶሎ ዩኒቨስቲ ተፈጽሞ የነበረውን አፈና በማንተራስ የሕዝብን ስሜት የሚያጎሽና ለአመጽ እንዲያነሳሳ የሚያድወርገው የብርቱካን ተመስገን ዶክመንታሪ ፊልም በኤርትራዊው ባለንብረት ኢቢኢኤስ ቲቪ መተላለፉን የሚያስታውሱት የመረጃ ምንጮች፣ ” ትንሽ እውነት ላይ በማንተራስ የተሰራው ድራማ ቢሳካ ኖሮ ሊደርስ የሚችለውን አደጋ ከፍተኛ መሆኑን ያስታውሳሉ።
ብርቱካን ተመስገን እንድትሰራው የተዋቀረው ሴራና በሴራው ላይ የተባበሩ ተዋንያኖች፣ እንዲሁም የቴሌቪዥኑ ባለቤት እንደመሰከሩት። ከዚያም በላይ መዐዛ መሐመድና ባልደረባዋ ከብርቱካን ጋር ያደረጉት የስልክ ልውውጥ ይፋ መሆን ብዙ እንዳስተማረ በርካቶች መናገራቸው አይዘነጋም። ድራማውን አጥንታ ለህዝብ ስታቀርብ እንባ ያራጨችው ብርቱካን፣ ሳይውል ሳያድር በዛው አንደበቷ የድርሰቱን ሃሰተኛነት ስትገልጸው ” በፍርድ ቤት የተያዘ ጉዳይ እንዴት ፊት ለፊት ይቀርባል” በሚል የመብትና የሕግ ተሟጋች የሆኑ ሚዲያዎችና ግለሰቦች የዚሁ ሴራ አካል እንደነበሩ ሕዝብ በይፋ መረዳቱ አይዘነጋም።
በሻዕብያ መሪነት ኢትዮጵያ ላይ እንዲረጭ ታስቦ የሚዘጋጁት ሰነዶች በ”ሰበር” በቅብብል እንዲበተን የሚደረገው ዝግጅት እንዳለ ሆኖ በሌላ በኩል የጦርነት ዝግጅቱ መቀጠሉ እየተሰማ ነው። የጦርነቱን ዝግጅት እያፋፋመ ያለው ሻዕቢያ ፋኖና ትህነግን ይዞ “ሰሜኖቹ” በሚል ጦርነቱን ትግራይና አማራ ክልል ላይ ለማድረግ ደፋ ቀና በሚልበት በአሁኑ ወቅት ” ጦርነት በቃን” የሚሉ መበርከታቸው ሌላ ተግዳሮች እንደሆነ እየተሰማ ነው። በተለይም የትህነግንና የሻዕቢያን “ግርድና ላይ የተመሰረተ” በሚል የሚታወቀውን አዲስ ፍቅር በመቃወም በብዛት ወደ አፋር ክልል ያፈገፈጉ የቀድሞ የትግራይ ተዋጊዎች ጉዳይ ለሻዕቢያ ራስ ምታት ሆኖበታል።
ካለፈው ጦርነት ፍርሃትና ህመም ያላገገሙ የትግራይ ነዋሪዎች ጦርነት እንደማይፈልጉ እያስታወቁ ባሉበት፣ የጦርነት ስጋት ላይ መሆናቸው በሚነገርበት ወቅት “ተፋናቃዮችን ወደ ቀያቸው ለመመለስ ሸቀጥና ነዳጅ ያስፍለገናል” ሲል ለመንግስትና ለዓለም ሕዝብ ድምጹን ያሰማው ደብረ ሽዮን የሚመሩት ትህነግ፣ በሕዝብ ስም ለኢትዮጵያ እየደገሰ ላለው ጦርነት ግብዓት የማሰባሰብ ስራ እየሰራ ነው” በሚል እየተተቸ ነው።
በራማና በዛላንበሳ በኩል በርካታ የጭነት መኪኖች ሸቀጥ፣ የታሸገ ቡና፣ ነዳጅና ምግብ። ፍራሽና የተለያዩ የዕለት ተዕለት ፍጆታዎችን ከመሃል አገር በትግራይ ሕዝብ ስም በማጋጋዝ ወደ ኤርትራ እንደሚተላለፍ በመስል ማስረጃ ምስክሮች እያጋለጡ ነው።
ከትግራይ ወደ ኤርትራ የሚደረግ ህገወጥ የሸቀጥ ዝውውር በአስቸኳይ እንዲቆም ዜጎች መቃወማቸው ብቻ ሳይሆን በኢትዮጵያ ለሚታየው የኑሮ ውድነት ተጨማሪ ችግር ሆኗል። ዶላር ከመልቀም ጀምሮ ቢትዮጵያ ኢኮኖሚ ላይ የሻዕቢያ አፍራሽ ሚና ከፍተኛ በመሆኑ አጋጣሚውን በመጠቀም መንግስት መርህ አልባ የሆነውን የኤርትራዊያን እንቅስቃሴና አኗኗር መላ ሊፈልግለት እንደሚገባ አንዳንድ የተቃዋሚ ድርጅቶች በይፋ እየጠየቁ ነው። ከዕለት ወደ ዕለት ጥያቄው የሕዝብ እየሆነም ነው።
በራማ በኩል ወደ ኤርትራ የሚጋዝ ሸቀጥና ነዳጅ የሚያሳይ ምስል አስደግፈው መረጃ የሰጡ፣ ከመሃል አገር ሸቀጥ ማጋዝና ከመንግስት በጀት የሚላክ ነዳጅ፣ መድሃኒትና፣ ቡና ፣ የታሸጉ የምግብና የመጠጥ ሸቀጦች ፣ ጥራጥሬ፣ ፍራሽ ወዘተ ተመሳሳይ ሸቀጦች በሸራሮ በኩልም እየተሻገረ መሆኑን ደጋግመው ቢናገሩም ከኢትዮጵያ ህዝብ ካዝና የሚቀለበው ትህነግ ህግ ማክበር ባለመቻሉ ንጹህ የትግራይ ዜጎቻችን እየተጎዱ መሆኑ ሊታሰብበት እንደሚገባም የሚያሳስቡ እየበረከቱ ነው።
አፋር ክልል ላይ እንዲቆሙ የታዘዙ መኪኖችን አስመልክቶ የጭነት ተሽከርካሪዎቹን ምስል በማንሳት ዜና ያደረጉ፣ በጠራራ ጸሃይ ወደ ኤርትራ እየተጋዘ ያለውን ሸቀጥ ምስል አስደግፈው ቢልኩም ዜናውን የሰሩት አካላት አላካተቱትም። ይልቁኑም መንግስት የትግራይ ሕዝብን እንደበደለ በማስመሰል ፕሮፓጋንዳ እየሰሩ ነው። የሻዕቢያንና ወያኔን ሴራ በቁሳቁስ አቅርቦት ለማሳደግ እየተጣደፉ ነው።
ከፍርሃቻ በመነሳት “ኦሮሞን ጥሉልኝና መንግስት እንገልብጥ” የሚል ጥሪ ያቀረቡት አቶ ኢሳያስና ትህነግ የነደፉት ሙሉ ዕቅድ ከነ አፈጻጸሙ መንግስት እጅ መግባቱን የሚያውቁ እንደሚሉት ኢሳያስ በከፍተኛ ደረጃ ሰግተዋል።
ልክ በትግራይ ንጹህ ወገኖች ጦርነት እንዳይነሳ እንደሚሰጉ ሁሉ፣ ኢሳያስም መንግስት ያነሳው የባህር በር ጉዳይ በዲፕሎማሲያዊ፣ በህጋዊ፣ ሰላማዊና ፍትሃዊ አግባብ እንደሚፈጸም፣ የኣለም አገራት ኢትዮጵያ ይህንን መብቷን ልተገኝ እንደሚገባት አምነው አቋም የያዙበት ጉዳይ በመሆኑ ወደ ጦርነት የሚያስገባ ሰበብ አለመኖሩ ሻዕቢያን አስጨንቆታል።
አካሄዱን የሚተነትኑ እንደሚሉት ሻዕቢያ አሁን ላይ የኢትዮጵያን አቅም መቋቋም ስለማይችል የአማራና የትህነግ ኃይሎችን ማስተባበሩ ምን አልባትም መንግስትን ወደ ድርድር ለመግፋት ከመሆን እንደማያልፍ እየገለጹ ነው።
ኢትዮጵያ የባህር በር ከሶማሊላንድ የምታገኝበት አግባብ፣ ሶማሊላንድ ዕውቅና ለማግኘት ዳር ከመድረሷ ጋር የሚቋጭ ከሆነ ኢሳያስም ሆነ ኤርትራ ስለ ኢትዮጵያ የሚያወሩበት አጀንዳ ስለማይኖር ትህነግና የአማራ ኃይሎች አደባባይ ላይ ሊሸጡ እንደሚችሉ የቀድሞ ጄነራል ሰሞኑን በተደጋጋሚ በአሃዱና በኢቲቪ መናገራቸው ይታወሳል።
ሻዕቢያ ያለውን ኃይል መዝኖ ጦርነት እንደማያዋጣው መገምገሙን ውስጥ አዋቂዎችን ጠቅሰን መዘገባችን ይታወሳል፡፡ በዚሁ ዘገባ “እመኑ ሻዕቢያ አንድ ጥይት አይተኩስም” ሲሉ የመረጃው ሰው ተናግረው ነበር።